INFORMATIE EN GEGEVENSVERZAMELING VOOR ONAFHANKELIJKE TIGRAY

ኣብዚ ገጽ እዙይ ብተጋሩ ልተጽሓፈ ተግንዩ

ዝርዝር ኣዋርሕ ኣብ ጎኒ እኒሀኩም። መጀመርታ ወርሒ ምረጹ ድሕሪኡ ልትደልዩዎ ኣረስቲ (ጽሑፍ) መሪጽኹም ኣንብቡ።

የፓርላማ ውሎ ፡- ጠቅላይ ሚንስተሩ ምን አሉ?

በዘመንፈስ አክሱማዊ

ከሰሞኑ ጠቅላይ ሚኒስተሩ ወደ ፓርላማ ብቅ ብለዋል፡፡ በዚህ የፓርላማ ውይይታቸው ጦርነት ላይ የተደገፈውን መንግስታቸውን ከኤኮኖሚም ከፖለቲካውም አንፃር ለማሳየት ሞክረዋል፡፡ የተውካዮች ምክር ቤት የስብሰባውን አላማ መሰረት አድርገው የተለያዬ አስተያየት እየተሰጠው ነው፡፡ ለአንዳንዶች የምክር ቤቱ ስብሰባ አላማ ጠቅላይ ሚንስተሩ ጦርነቱንም እድገቱንም አሳካሁ ብሎ ለመናገር የተጠቀሙበት የማስተወቂያ መድረክ ነው፡፡

በዚህም መድረክ ላይ ጠቅላይ ሚንስተሩ በፓርላማው አባላት ጦርነት ያሸነፉ፤ አገር ከብተና ያዳኑ ፤ የአባይን ግድብን ስራ ያስጀመሩ ተብለው በተጋነነ መንገድ ተሞካሽተውበታል፡፡ እሳቸውም ጦርነቱንም ኤኮኖሚውንም መሳ ለመሳ አሳክቻለሁ በሚል ግላዊ ገፅታቸውን ለመገንባት ተጠቅመውበታል፡፡

ከጠቅላይ ሚንስተሩ የገፅታ ግንባታ አላማ ጎን ለጎን ምክር ቤቱ ራሱ አገር ሰላም መሆኑና የተረጋጋች መሆኗን ለማሳየት እንደ ምክር ቤትም አለሁ የሚለውን ገፅታ ለዜጎችም ለአለምም ለማስተዋወቅ ተጠቅሞበታል፡፡ በዚህ የምክር ቤት ስብሰባ ላይ ጠቅላይ ሚንስተሩ ብዙ አውርተው የተከበረው የምክር ቤት አባላት በጥቂቱ ጠይቀው ተጠናቋል፡፡

ለመሆኑ ጠቅላይ ሚንስተሩ ምን አሉ?

የጦርነት ኤኮኖሚ

ጠቅላይ ሚንስተሩ አገሪቱን ወደለየለት ጦርነት አስገብተው ስለኤኮኖሚ ችግር ሲያወሩ የአገሪቱ መሪ አይመስሉም፡፡ ጦርነቱ ብዙ ችግሮች መፍጠሩን አልደበቁም፡፡ “በውጊያ ጊዜ የሚኖር የኤኮኖሚ ግንባታ ዘርፈ ብዙ ፈተናዎች አሉበት፡፡ ውጊያ ሲካሄድ ብድር የሚሰጡ ወገኖች ብድራቸውን ያዝ ያደርጋሉ፡፡ እርዳታ የሚሰጡም እርዳታቸውን ያዝ ያደርጋሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ አመራሩ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩር በመሆኑ የልማት ስራዎች ይስተጓጎላል፡፡

ስለዚህ እርዳታና ድጋፍ ብቻ ሳይሆን አመራር ያታል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ መፈናቀል አለ፡፡ ሰዎች ይገደላሉ፡፡ ይሰደዳሉ፡፡ ይፈናቀላሉ፡፡ አምራቹም በአካልም በሓሳብም ልቡ ወደ ጦርነት ይሸፍታል ” በሚል ብዙ ችግሮችን ደርድረዋል፡፡ ድርቁም እንደተጠበቀ ሆኖ ስለዚህ በጦርነት የሚደረግ ኤኮኖሚ ግንባታ አስቸጋሪ ነው ብለዋል፡፡

ይህንን የሰሙ ታዛቢዎች “ይህን ሁሉ የጦርነት ቀውስ የፈጠረው ማን ነው?” ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡ ጠቅላይ ሚንስትሩ ግን ይህን ሁሉ ችግር ራሳው አንዳልፈጠሩት አድርገው እዳር ቆመው ነው ችግሩን ራሱ የወቀሱት፡፡ ራሱ ተኩሶ ራሱ ይጮሀል እንደሚባለው ጠቅላይ ሚንስተሩም ራሳቸውን የፈጠሩት ችግሮች ራሳቸው የሌሉበት ይመስል በፓርላው ሲጮሁ ተስምተዋል፡፡

የሆነው ሆኖ ጠቅላይ ሚንስተሩ ጦርነትም እያለ የአገሪቱ ኤኮኖሚ እያደገ መሆኑን ነግረውናል፡፡ በጤነኛ አገር ኤኮኖሚና ጦርነት አንድ ላይ አይሄዱም፡፡ እርስ በእርስ የሚጋጩ ናቸው፡፡ በተአምረኛዋ የጠቅላይ ሚንስተሩ አገር ግን ጦርነቱ የአገሪቱን ኤኮኖሚ አሳድጎታል፡፡

ይኼ ለብዙዎች የሚያስቅም የሚገርምም ጉዳይ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ አገሪቱ በሰላሙ ጊዜ ያልፈጠረችውን ይህን ያህል እድገት በጦርነት ወቅት እንዴት ልታሳካ ቻለች የሚለው ብዙዎችን ያጠያየቀ ጉዳይ ነው፡፡

አርሶ አደሩን ወደ ጦርነት ማግደው ፤ የአርሶ አደሩን እርሻ የጦር አውድማ አድርገው ግብርናው ባቀድነው መሰረት መቶ በመቶ አድጓል አሉ፡፡ ፖለቲካው ለግብርና አመቺ ባልሆነበት አርሶ አደሩ ሚሊሻ ፤ እርሻው የጦር አውድማ በሆነበት በእቅዳችን መሰረት የግብርና ልማቱ መቶ በመቶ አድጓል ካሉ መጀመሪያ አላቀዱም ነበር የሚያስብል ነው፡፡ ጠቅላይ ሚንስተሩ በኤኮኖሚ ሪፖርታቸው በአብዛኛው ኢምፖርት ማደበሪያ ነው ባሉበት ንግግራቸው ኢምፖርቱ የጦር መሳሪያን መሆኑን ረስተዋል፡፡ ከኤኮኖሚው አገራቸው ያመረተችው አብዛኛው የገቢ ምንጭ የወታደርና የልዩ ኃይል ዩኒፎርም መሆኑን ግን አልደበቁም፡፡ ይሄ አንድ ነገር ነው፡፡

የኢትዮጵያ አየር መንገድን የሰርቪሱ እድገት ማሳያ አድርገው አቅርበዋል፡፡ ጠቅላይ ሚንስተሩ አየር መንገዱ አገር ኩራት ከመሆኑም በላይ የሰርቪሱን ኤኮኖሚ እድገት ላይ ገንቢ አስተዋፅኦ ማድረጉን ተናግረዋል፡፡ ይህንን በተናገሩበት ሪፖርት ግን አየር መንገዱ የጦር መሳሪያዎችን በገፍ በማጓጓዝ ጦርነቱን በማቀጣጠል በኩል የነበረውን አተራማሽ ሚና አልነገሩንም፡፡ ጠቅላይ ሚንስተሩ ከራሳቸው አንፃር ኤኮኖሚውን መለካታቸው ስኬታማ እንዲሆኑ አስችሏቸዋል፡፡ ለትንታኔዎቻቸው የኤኮኖሚ ንድፈ አሳብ ብዙም ያልተጠቀሙት ጠቅላይ ሚንስተሩ የአገሪቱንም የኤኮኖሚ ችግር በተጨባጭ ይፍታ አይፈታ በግልፅ አላሳዩም፡፡ ሰውየው ኤኮኖሚው አድጓል ያሉት እድገቱን ከራሳቸው መለኪያ አንፃር በመለካት ብቻ ነው፡፡

በዚሁ የኤኮኖሚ ሪፖርታቸው የዋጋ ግሽበቱን በሚመለከት የችግሩ መነሻ የፍላጎት መጨመርን እንደ ምክንያት ማንሳታቸው ከቀድሞ ኢህአዴግ ጋር ያመሳስላቸዋል፡፡ በአጠቃላይ የኤኮኖሚ እድገቱ ጦርነትን የሚያስረሳ በመሆኑ ሪፖርቱ የኢህአዴግ ነው የእሳቸው የሚል ጥያቄ ያስነሳል፡፡

ፖለቲካውስ?

የጠቅላይ ሚንስተሩን ንግግር ከፖለቲካ አንፃር ካየነው ጦርነቱና ጦርነቱ ያሰከተለውን የኤኮኖሚ ጉዳት እርሱትና እኔ ስልጣኔን ልቀጥል የሚል አይነት ነው፡፡ ጦርነቱን እርሱ እና መጪውን ጊዜ ስለብልፅግና እያወራን ስልጣኔን አራዝሙልኝ የሚል ስሜት ያለው ነው፡፡ ከአንዳንድ የፓርላማ አባላት ግለሰቦች ይታሰሩልኝ የሚል ጥያቄ ጭምር መነሳቱ ፓርላመው ጊዜውን ሲያባክን የነበረው አሉባልታ የሚመስል ጉዳይ ላይ መሆኑን እንድረዳ አድርጎኛል፡፡

የድርድር ጉዳይን በተመለከተ እስከአሁን ድርድር የለም ብለዋል፡፡ ነገር ግን ድርድር የለም ማለት ድርድር አይኖርም ማለት አይደለም በሚል ያው ዞሮ ዞሮ ድድርድር መኖሩን አመላክተዋል፡፡ ድርድር የሊህቃን ድርድር ሊሆን አይችልም ያሉት ጠቅላይ ሚንስተሩ የሊህቃን ድርድር ደግሞ ስልጣንን መሰረት ያደረገ ነው በሚል ተችተዋል፡፡ “ስልጣኑ የተሰጠው ደግሞ ለብልፅግና ነው፡፡

ብልፅግና ለአራት አመት በህዝብ ተመርጧል” በሚል ስልጣን የምትፈልጉ ቁርጣችሁ እውቁ አይነት አሳብ ሰንዝረዋል፡፡ ይሄ ዞሮ ዞሮ ብልፅግናም ድርድሩን የሚፈልገው ስልጣኑን ለማስቀጠል መሆኑን ጠቅላይ ሚንስተሩ ሊህቃኖቹን ከተቹበት አሳብ መውሰድ አንችላለን፡፡ በዚህም ጠቅላይ ሚንስተሩ ስልጣናቸው እስካልተነካ ድረስ በማንኛውም ጉዳይ ላይ እንደሚደራደሩ ያመላክታል፡፡

በሌላ በኩል የፖለቲካ ችግሩ መነሻ የእሳቸው ስልጣን መሆኑን ለሚያምኑ ሰዎች ድርድሩ በሌሎች ጉዳዮች ላይ እንጂ በስልጣን ላይ እንዳልሆነ አስረግጠው አልፈዋል፡፡ ውይይት ወይም ድርድር የሚያስፈልገው የፖለቲካ ቀውስ ሲኖር ፤ ከጦርነት በኋላ እና የፖለቲካ ሽግግር ላይ ነው ብለዋል፡፡ እነዚህ ችግሮች ደግሞ በአገሪቱ መኖራውን አልካዱም፡፡

ድርደሩ ወሳኝ የሚሆነው የፖለቲካ ቀውሱን ለመፍታት፤ ጦርነቱን ለማርገብና የጠቅላይ ሚንስተሩ ስልጣን የሚደላደልበትን የፖለቲካ ሽግግር ለመፍጠር ነው በሚል ከንግግራቸው መውሰድ እንችላለን፡፡ ስለዚህ ድርድሩ ወሳኝ የሚሆነው የጠቅላይ ሚንስትሩና የፓርቲያቸው ስልጣን እስካልተነካ ድረስ ነው፡፡

በዚህም ተባለ በዛ የጠቅላይ ሚንስተሩ ስልጣን እስካልነተካ ድረስ ጠቅላይ ሚንስተሩ ለድርድር ዝግጁ መሆናቸውን ንግግራቸው ያሳብቃል፡፡ ድርድሩን ለኢትዮጵያ ሲባል ቢሉም ኢትዮጵያንና ስልጣናቸውን ለያይተው ለማያዩ ሰዎች ግን ሰውየው በስልጣኑ እንደማይደራደር ታዝበዋል፡፡

ትግራይና የጦርነቱ ጉዳይ

በትግራይ ጉዳይ ላይ ጠቅላ ሚንስተሩ ውሸትም ማስመሰልም በእጅጉ የጎላበት አሳብ ሰጥተዋል፡፡ በአንድ በኩል በከበባ ችግር ለሚያሰቃዩት ለትግራይ ህዝብ አሳቢና ተቆርቋሪ ሆነው አስመስለዋል፡፡ የጦርነቱን መነሻ እንደተለመደው መከላከያ ስናጓጉዝ ህፃናት አስተኝተው አስቆሙን ከዚያ በኋላ ደግሞ ቀጠቀጡት የሚለውን የተለመደ ፕሮፖጋንዳ ሲነዙ ተስመተዋል፡፡

ጦርነቱ ላየ ግን ከጥፋቱ በኋላም ቢሆን የገባቸው ይመስላል፡፡ በእረስ በእርስ ጦርነት ፍፁም የሆነ ድል የለም ብለዋል፡፡ ይህንን አስቀድመው የህወሓት አመራሮች በተደጋጋሚ ሲናገሩት እንደፈሪ የተቆጠሩበትን ምክንያት ነው ዛሬ ጠቅላይ ሚነስተሩ በአደባባይ የተናገሩት፡፡ ፍፁም ድል ከሌለ ጊዜያዊ ድል ነው የሚኖረው ብለው የቀጠሉት ጠቅላይ ሚንስተሩ እኛ የምንፈልገው በቂ ድል ነው ብለዋል፡፡ እነዚህን ድሎችስ ቢሆን በትክክል አግኝተዋል ወይ የሚል ጥያቄ ግን ያነሳላቸው የለም፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ ራሳቸውን የሰላም እና የውይይት ሰባኪ ሌሎች ኃይሎችን (በአብዛኛው ህወሓትንና ኦነግ) ጦር ሰባቂ አድርገው አቅርበዋል፡፡ በተለይም ደግሞ በከባባ አዲስ ጦርነት ችግር ውስጥ የከተቱትን በየጊዜው በድሮን ድብደባ የሚቀጠቅጡትን የትግራይ ህዝብ ተቆርቋሪ ሆነው መቅረባቸው ብዙዎችን አስገርሟል፡፡ የትግራይ ህዝብ መድሀኔት የለውም፡፡

የትግራይ ህዝብ መብራት የለውም ማለታቸው እንዳኖረው ያደረኩት እኔ ነኝ ከማለት አይተናነስም፡፡ በዚህ አስመሳይ ንግግራቸው መንገድ የዘጉበትን ህዝብ መንገድ አልዘጋንም በሚል ችግሩን ወደ ትግራይ ህዝብ ለሚታገለው ህወሓት ወርውረዋል፡፡

በዚህ የማስመሰል ተቆርቋሪነታቸው የምክር ቤት አባላቱን የትግራይ ህዝብ ጥያቄ ለምን እንደማያነሱ ወቅሰዋል፡፡ ይህ አካሄዳቸው ደግሞ በአውነት ለትግራይ ህዝብ ተቆርቁረው ሳይሆን ያኮረፈውን የትግራይ ህዝብ አንጀት ለመብላት ፤ ለሰላም ዝግጁ መሆናቸውን እንዲያውቅላቸው ማድረግ ላይ የተመሰረተ የፖለቲካ ትርፍ ላይ ያለመ ነው፡፡ ጠቅላይ ሚንስተሩ በዚህ መልኩ ተቆርቋሪ ሆነው ለመታየት ቢሞክሩም እሳቸው በፈጠሩት ዘርፈ ብዙ ችግሮች አሁንም የትግራይ ህዝብ እየተሰቃየ ነው፡፡

የካቲት 20/2014 ዓም
ድምፂ ወያነ ትግራይ

Read More